Joomla TemplatesBest Web HostingBest Joomla Hosting

Government Statement

ሳምንታዊ የአቋም መግለጫ09/09/05

ውብ አዲስ አበባን የመፍጠር ራዕያችንን ምቹ የመኖሪያ ቤቶችን ለነዋሪዎች ለማስተላለፍ እቅዳችን በተጠናከረ ሁኔታ በተግበር እናረጋግጣለን

 

መዲናችን አዲስ አበባ ለዘመናት ተከማችተውባት በኖሩ ዘርፈ ሰፊ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች አማካኝነት እድገቷ ተገቶ ቆይቷል፡፡

የአፍሪካና የአለም አቀፍ ተቋማት መገኛ የሆነችው ከተማችንን የተጋረጡባትን የእድገት ማነቆዎች በመበጣጠስ በልማት ጎዳና ላይ መገስገስ ጀምራለች

በህዝቦች ተጋድሎ ዲሞክራሲያዊና ሕገ መንግስታዊ ስርአቷን ያፀናቸው ሀገራችን ከዳር እስከ ዳር ያቀጣጠለችው የልማት ችቦ ከተማችንንም ማሞቅ እና ማድመቅ ከጀመረ እነሆ ጥቂት አመታት መቆጠር ጀምረዋል፡፡

በተለይም ካለፉት አምስት አመታት ወዲህ ከተማችን አዲስ አበባ በሁሉም የልማት ዘርፎች የጀመረቻቸው ስር ነቀል ለውጦች ውጤት ማስመዝገብ ይዘዋል፡፡

መዲናችንን ውብ፣ ምቹና ለኑሮ ተስማሚ ለማድረግ አስተዳደሩ በያዘው ትግል ያረጁና የተጎሳቆሉ የከተማዋን ስፍራዎች በአዲስ ለመለወጥ ተስፋ ሰጪ እምርታዎች ማስተዋል ተችሏል፡፡

ከተማችን አዲስ አበባ ከሀገራችን ከተሞች በተሻለ ደረጃ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ የሚፈስባት ከተማ መሆንዋ ይታወቃል፡፡ የዚህ ካፒታል መሰረቱም የመዲናችን ነዋሪዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም በከተማችን ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል እንዲኖር ማስቻልና ይህንንም ፍትሐዊነት በህዝቡ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ይገባል፡፡ ስለሆነም የከተማችን ነዋሪ ዋንኛ ጥያቄ የሆነውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመፍታት መንግስት እያደረገ ያለውን እንቅስቃሴ በተለያየ መንገድ አጠናክሮ ቀጥሏል፡፡

የከተማችን ነዋሪዎችን የዘመናት የመኖሪያ ቤት እጦት ጥያቄን ለመፍታት አስተዳደሩ ባደረገው ያላሰለሰ ትግል ባለፉት ጥቂት አመታት ብቻ ከ1ዐዐ ሺህ በላይ የመኖሪያ ቤቶችን በመገንባት ለተጠቃሚዎች አስተላልፏል፡፡ በዚህም ግማሽ ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎችን የመጠለያ ጥያቄ መፍታት ተችሏል፡፡

በአሁኑ ወቅትም ከ95 ሺ በላይ ቤቶች በግንባታ ላይ ያሉ ሲሆን ከነዚህ ውስጥ ያልተላለፉ ከ89 ሺህ በላይ ቤቶችን በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ ነዋሪዎችም ከ24 ሺህ በላይ የሚሆኑ ቤቶችን በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡

በዚህ ዘርፍ አስተዳደሩ እስከ አሁን ከ2 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ ያደረገ ሲሆን የመረሃ ግብሩ የጎንዮች አላማ በሆነው የስራ ዕድል ፈጠራ ከ148 ሺ በላይ ለሚደርሱ ወገኖች በተለያየ ደረጃ የስራ ዕድል መፍጠር ተችሏል፡፡

አስተዳደሩ በከተማችን ለዘመናት የተከማቸውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመፍታት በ1996 በጀመረው የተቀናጀ የመኖሪያ ቤት ግንባታ በርካታ የመዲናችን ነዋሪ ተጠቃሚ ማድረግ የቻለ መሆኑ የአደባባይ ሀቅ ነው፡፡

ይሁን እንጂ ከከተማዋ እድገትና ልማት ጋር በተያያዘ የሚነሳው የመኖሪያ ቤት ጥያቄ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ አስተዳደሩ ሌሎች የተሻሉ አማራጮችን በመቅረፅ የሕብረተሰቡን ችግር ለመቅረፍ ይበልጥ እንዲንቀሳቀስ አድርጓታል፡፡

በመሆኑም ቀደም ተብሎ ከተጀመረው 2ዐ/8ዐ የተቀናጀ የመኖሪያ ቤት ግንባታ ጎን ለጎን ድሃ ተኮር የሆኑ የ1ዐ/9ዐ ቤቶችና ለመካከለኛ ገቢ ያላቸው ነዋሪዎችን የሚያቅፉ የ4ዐ/6ዐ እና የሕብረት ስራ የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ ማህበራትን ያካተቱ የመኖሪያ ቤት መርሃ ግብሮችን በመቅረፅ በቅርቡ የከተማችንን ነዋሪ ተጠቃሚ ለማድረግ የምዝገባ ስራውን በአዲስ መልክ ለማካሔድ ዝግጅት መጀመሩ ይታወቃል፡፡

አስተዳደሩ በእነዚህ የመኖሪያ ቤት ልማት ኘሮግራሞች ነዋሪው ተጠቃሚ የሚሆኑበትን እድል ያመቻቸ ሲሆን ዜጎች ተገቢና ፍትሐዊ የሆነ የሀብት ክፍፍል ቀጥተኛ ተጠቃሚዎች በማድረግ የሀገራችንን እድገት ለማፋጠን እየሰራ ይገኛል፡፡

ከዚህ ጎን ለጎን የከተማችን ነዋሪዎችን በተለይም አነስተኛና መካከለኛ ገቢ ያላቸውን የሕብረተሰብ ክፍሎች በዋናነት የገቢ አቅማቸውን በማሳደግ እና ከገቢያቸው በመቆጠብ የቁጠባ ባህላቸውን እያሳደጉ የቤት ችግሮቻቸውን መፍታት የመርሃ ግብሩ ሌላኛው አላማ ነው፡፡

አስተዳደሩ ቀደም ብሎ የከተማዋን ነዋሪዎች የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ባደረገው እንቅስቃሴ በ1997 ዓ/ም 453 ሺህ የሚሆኑ አመልካቾችን በመመዝገብ ከ1ዐዐ ሺህ ያላነሱት የመኖሪያ ቤት በመገንባት ማከፋፈሉ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ይህ ምዝገባ ከተካሔደ በኋላ በሚፈጠሩ ተፈጥሮአዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጦች አማካኝነት ቀሪዎቹ ተመዝጋቢዎች ያሉበትን ሁኔታ በዳግም ምዝገባ ማጥራት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡

ስለሆነም በወቅቱ የተመዘገቡ እና የመኖሪያ ቤት እድሉ ያልደረሳቸው ዜጎች በነባር አመልካቾች ምድብ ለ2ዐ/8ዐ የመኖሪያ ቤት መርሃ ግብር ዳግም የሚመዘገቡበት ስርአት ተዘርግቷል፡፡

ሌሎች አዲስ ተመዝጋቢዎች አስተዳደሩ ካዘጋጃቸው አራት አማራጮች ማለትም የ1ዐ/9ዐ ዝቅተኛ የወር ገቢ ላላቸው ነዋሪዎች የ2ዐ/8ዐ አነስተኛ ገቢ ላላቸው ነዋሪዎች፣ የ4ዐ/6ዐ መካከለኛ ገቢ ላላቸው ነዋሪዎች እና በህብረት ስራ ማህበራት የመኖሪያ ቤቶችን መገንባት በሚሉ ምድቦች ውስጥ አቅምንና ፍላጎትን በማመዛዘን በአንዱ ላይ ብቻ በመመዝገብ የመርሃ ግብሩ ተጠቃሚ መሆን ይችላሉ፡፡

አስተዳደሩ የነዋሪውን ችግር ለመፍታት በዘረጋቸው የመኖሪያ ቤት ግንባታ መርሃ ግብሮችን ተግባራዊ ለማድረግ ላለፈው አንድ አመት ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡

በዚህም ዝግጅት ምዝገባው የሚመራበትን መመሪያ ከማውጣት ጀምሮ ምዝገባው የሚካሔድበትን ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን መቅረፅ ችሏል፡፡

በመሆኑም የምዝገባውን ስርአት አስመልክቶ በከተማዋ ሁሉም ወረዳዎች ለሚገኙ አራት ሺህ ለሚሆኑ ኃላፊዎች፣ አስተባባሪዎችና ባለሙያዎች ስልጠና ተሰጥቷል፡፡ ከ15ዐዐ በላይ ዳታ ኢንኮደሮች በኮምፒውተር ቴክኖሎጂዎች ማዘጋጀት ተችሏል፡፡

በዚህም ምዝገባውን በከተማዋ ሁሉም ወረዳዎች ወጥነት ባለው መንገድ ማካሔድ የሚያስችል ዘመናዊ ቴክኖሎጂ መዘርጋት ተችሏል፡፡ ለዚህም ስራ አስተዳደሩ ከ11 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ በማድረግ የሕብረተሰቡን መረጃ በአስተማማኝ እና በተቀላጠፈ መልክ ማደራጀት የሚያስችል ስርአት አዋቅሯል፡፡

የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ችግርን ለመፍታት አስተዳደሩ እያካሔድ ባለው በዚህ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ውስጥ የከተማችን ነዋሪ የተለመደ ድጋፉን በማበርከት ለመርሃ ግብሩ ስኬት የበኩሉን አስተዋጽኦ ማበርከት ይጠበቅበታል፡፡

በዚህም በቀጣዩ ሰኔ 3 ቀን 2ዐዐ5 ዓ/ም በይፋ ምዝገባው በሁሉም የከተማችን ወረዳዎች የሚጀመረውን የ1ዐ/9ዐ እና የ2ዐ/8ዐ የነባር እና አዲስ የመኖሪያ ቤት አመልካቾች ምዝገባ ከመካሔዱ በፊት ቅድመ ዝግጅቶችን በማድረግ ምዝገባውን በሰከነ እና በተረጋጋ ሁኔታ ማካሔድ ይኖርበታል፡፡

ነዋሪዎች ለምዝገባው የሚያስፈልጉ መስፈርቶችን በአግባቡ በመረዳት ቀደም ካለው አስፈላጊ የሆኑ መረጃዎችን ማለትም የነዋሪነት ማረጋገጫ የመታወቂያ ወረቀት፣ የቁጠባ ማረጋገጫ የባንክ ደብተር እንዲሁም የትዳር ሁኔታዎችን የሚጠቁሙ ማስረጃዎችን በማጠናከር ምዝገባው የተቀላጠፈና የተሳካ እንዲሆን የበኩላቸውን ድጋፍ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ምዝገባዎቹ በቅደም ተከተል የሚካሔዱ ሲሆኑ ከሰኔ 3 እስከ 2ዐ የሚካሔደው የ1ዐ/9ዐ እና የ2ዐ/8ዐ መርሃ ግብር ምዝገባ መጠናቀቅ በኋላ በቀጣይ የሐምሌ ወር አጋማሽ የመኖሪያ ቤት ማህበራት ምዝገባ ይካሄዳል፡፡በመቀጠልም በቀጣዩ የነሐሴ ወር የ4ዐ/6ዐ የመኖሪያ ቤት መርሃ ግብር ምዝገባ እንደሚካሔድ ይጠበቃል፡፡

ስለሆነም ዜጎች አስቀድመው አቅማቸውን በመፈተሽ ከመርሃ ግብሩ በአንዱ ላይ ብቻ እንዲመዘገቡ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

የከተማ አስተዳደሩ ከፊደራል መንግሥት ጋር በመተባበር በታላቁ መሪ የተቀየሰውን የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ ተግባራዊ ለማድረግ በመኖሪያ ቤት ግንባታ ዘርፍ የያዘውን 17ዐ ሺህ ቤቶች በእቅዱ ዘመን ገንብቶ በማጠናቀቅ ከ85ዐሺ በላይ ለዜጎች ለማከፋፈል የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡

መላው የከተማችን ነዋሪም የመዲናችንን ህዳሴ እውን ለማድረግ አሰተዳደሩ ከያዛቸው የልማት ስራዎች ጋር የተለመደ ትግሉን በማቀናጀት አዲስ አበባችን ለዘመናት የተከማቹባቸው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ከስሩ በመናድ መዲናችንን ውብ ምቹና ለኑሮ ተስማሚ የማድረግ ጥረታችንን በጋራ አጠናክረን እንድንቀጥል አስተዳደሩ በዚህ አጋጣሚ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

           የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

 

 

 

 

ሳምንታዊ የአቋም መግለጫ02/09/05

ህዝቡ በድምፁ ለልማት ስራዎቻችን የሰጠውን ይሁንታ አጠናክረን እናስቀጥላለን

 

ለአንድ ሀገር እድገት የዜጎች ቀጥተኛ ተሳትፎ ያለው ድርሻ ከፍተኛ ነው፡፡ ዜጎች በሀገራቸው ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የሚጫወቱት ሚና ለሀገሪቱ እድገት ወሳኝ ነው፡፡

ያለ ሕዝብ ተሳትፎ የሚመራ ልማት የተሟላ ሊሆነ አይችልም፡፡ በህዝቦች ፍላጎትና ተሳትፎ በፀደቀ ህገ መንግስትና ዲሞክራሲያዊ ስርአት በሚመሩ ሀገሮች ሕዝቦች ለሀገራቸው ልማት እና እድገት ይበጃሉ ያሉዋቸውን ተወካዮቻቸውን በዴሞክራሲያዊ መንገድ በመምረጥ የስልጣን ምንጭ ይሆናሉ፡፡ ተወካዮቻቸውም ይሁንታውን ለሰጣቸው ህዝብ ደህንነት፣ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት እንዲሁም ሰብአዊ መብቶችና ፍላጎቶች መሟላት የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት ይወጣሉ፡፡ ይህን ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ካልተወጡ የስልጣን ባለቤት የሆነው ሕዝብ ውክልናቸውን የሚነጥቅበት ሂደት ይፈጠራል፡፡

ሀገራችን ኢትዮጵያም በጭቁን ብሔር ብሔረሰቦች ተጋድሎ በተጎናፀፈችው ዴሞክራሲያዊ ስርአት አማካኝነት የህዝቡን ሉአላዊ የስልጣን ባለቤትነት የሚያረጋግጥ ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ማድረግ ከጀመረች ዋል አደር ብላለች፡፡

የሀገራችን ብሔር ብሔረሰቦች ባቀረቡትና ባፀደቁት ህገ መንግስታዊ ስርአት አማካኝነት ቋንቋ ባህልና ማንነታቸው ተከብሮ ለሀገራቸው እድገት በቁርጠኝነት መስራት ከጀመሩ ሁለት አስርተ አመታት ተቆጥረዋል፡፡

የሀገራችን ሕዝቦችም በቀጥተኛ ተሳትፎአቸው ይሁንታን በሰጧቸው መሪዎቻቸው አማካኝነት በልማት እና በእድገት ጎዳና ላይ ግስጋሴያቸውን አፋጥነዋል፡፡

ባለፉት አራት ሀገር አቀፍ ምርጫዎች መላው የሀገራችን ህዝቦች ሙሉ ተሳትፎ በማድረግ በዲሞክራሲያዊ መንገድ መሪዎቻቸውን መምረጥ ችለዋል፡፡ በመረጡዋቸው ተወካዮቻቸው

አማካኘነት የሀገራቸውን ህዳሴ የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን በስፋት እያካሔዱ ይገኛሉ፡፡

ሀገራችን ኢትዮጵያ ባሳለፍነው የሚያዚያ ወርም የከተማ አስተዳደር እና የአካባቢ ምርጫን እንደ ከዚህ በፊቱ ሁሉ የአለም አቀፍ የምርጫ መስፈርቶችን ባሟላ መልኩ በማካሔድ በተሳካ ሁኔታ ማጠናቀቅ ችላለች፡፡

በዚህ ምርጫም የከተማችን አዲስ አበባ ነዋሪዎችም የጀመሯቸው የልማት እና የእድገት ጉዞዎችን ያስቀጥላሉ፣የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎች በተሟላ መልኩ ይፈታሉ ብለው ያመኑባቸውን መሪዎቻቸውን በነፃነት እና በሙሉ ፍቃዳቸው መምረጥ ችለዋል፡፡

በዚህም የአዲስ አበባ አስተዳደር ከከተማ እስከ ወረዳ ባሉ የምርጫ ጣቢያዎች ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ በኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ አሸናፊነት ሊደመደም ችሏል፡፡

ይህም አስተዳደሩ ከህዝቡ ጋር ሲያደርግ የቆየው የልማት እንቅስቃሴ በህብረተሰቡ ዘንድ ያገኘው ተቀባይነት ከፍተኛ መሆኑን ያሳየ ነው፡፡ ህዝቡም ለከተማዋ እድገትና ልማት ከኢህአዴግ ጋር የበለጠ በመስራት የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ያለውን ቁርጠኝነት በምርጫው አሳይቷል፡፡

በድርጅታችን ኢህአዴግ መሪነት የአዲስ አበባ አስተዳደር ባለፉት አመታት የከተማዋን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ለመፍታት በተለይም በጥቃቅንና አንሰተኛ በመቶ ሺዎች ለሚቆጠሩ ዜጎች የስራ ዕድል በመክፈት ለራሳቸውና ለሀገራቸው እድገት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ አስችሏል፡፡

አስተዳደሩ የከተማዋን የንግድ እንቅስቃሴ ስርአት በማስያዝ በኩል ያከናወናቸው ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤት ማስመዝገባቸው በከተማዋ የሚስተዋለውን የኑሮ ውድነት ለማስተካከል እና የዋጋ ንረትን ለማርገብ የወሰዳቸው እርምጃዎች ትርጉም ያለው ውጤት ማስመዝገባቸው በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ ማግኘቱ ነዋሪው ለሰጠን ቀጣይ ኃላፊነት ዋና ምክንያቶች ናቸው፡፡

በማህበራዊ ጉዳዮችም በተለይም ጥራት ያለው ትምህርትን ለሁሉም ዜጎች በማድረስ ረገድ የተሰሩ ስራዎች፣ በጤና ኤክስቴንሽን የተመዘገቡ ለውጦች፣ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ረገድ የተጀመሩ ስራዎች እና በአካባቢ ውበትና ፅዳት እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች በህብረተሰቡ ዘንድ ተቀባይነት ማግኘታቸውን ያሳያል፡፡

ይህም ቢሆን ግን ገና ብዙ ቀሪ ሥራዎች እንዳሉብን ህብረተሰቡ በተለያዩ መንገዶች ገልጿል፡፡ በተለይም መልካም አስተዳደር ከማስፈን አኳያ በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከህዝቡ ጋር በመምከር የተጀማመሩ ስራዎች ቢኖሩም በተሟላ መልኩ መስራት እንደሚጠበቅብን እንረዳለን፡፡ የከተማችንን ልማትና እድገት ከማፋጠን ጐን ለጐን ለህብረተሰቡ ፈጣንና ግልፅ አገልግሎት መስጠት እንደሚገባን እንገነዘባለን፡፡

በተለያዩ ዘመናት በተቆለሉባት ዘርፈ ሰፊ ችግሮች ምክንያት አሮጌና ጐስቋላ የሆነችውን ከተማችንን መልሶ በማልማት ውብና ፅዱ ለማድረግ የተሰሩ ስራዎች ውጤት ማስመዝገብ መጀመራቸውን እንረዳለን፡፡

የከተማዋን መሠረተ ልማት በማሻሻል በተለይም አዳዲስ የባቡር መስመሮችን ጨምሮ ዘመናዊ እና ውብ የመንገድ ስራዎቻችን የሕብረተሰቡን ድጋፍ ማትረፋቸው የአደባባይ ሀቅ ነው፡፡

የከተማዋን የመኖሪያ ቤት ችገር ለመፍታትም ከ8ዐ ሺህ በላይ የሚሆኑ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን በመገንባት ለህብረተሰቡ ማከፋፈል ተችሏል፡፡ በአሁኑ ወቅትም ከ95 ሺህ በላይ የሚሆኑ የመኖሪያ ቤቶችን በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡ በዚህ መርሃ ግብር ከግማሽ ሚሊየን የሚለቁ ዜጐች የመኖሪያ ቤት ችግሮቻቸውን መፍታት ተችሏል፡፡

በአሁኑ ወቅትም አስተዳደሩ የጀመረውን የመኖሪያ ቤት እጥረት ችግርን ለመፍታት ከፍተኛ በጀት በመመደብ በተለያየ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ነዋሪዎችን ማስተናገድ የሚችሉ ልዩ ልዩ አይነትና መጠን ያላቸውን የመኖሪያ ቤቶች በመገንባት የነዋሪውን ጥያቄ ለመፍታት በመስራት ላይ ይገኛል፡፡

ለዚህም ነው የመኖሪያ ቤት ጥያቄ ለሚያቀርቡ እና ከዚህ ቀደም በተካሔዱ ምዝገባዎች ያልተመዘገቡ አዲስ ተመዝጋቢዎችን እና በመጀመሪያ ዙር ምዝገባ ተመዝግበው እጣ ያልደረሳቸውን በአዲስ መልክ በመመዝገብ የመኖሪያ ቤት ችግሮቻቸውን ለመፍታት አስተዳደሩ መነሳቱን ያስታወቀው፡፡

ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ በክቡር ከንቲባው አማካኝነት የተላለፈው የአዲስ የመኖሪያ ቤት ምዝገባ እድል የከተማችን ነዋሪ በአግባቡ በመጠቀም ለመዲናችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት የተያያዘውን ትግል አጠናክረን እንቀጥላለን፡፡

በአዲስ የመኖሪያ ቤት ምዝገባ ከዚህ ቀደም የተመዘገቡም ሆኑ አዲስ ተመዝጋቢዎች የሚካተቱ ሲሆን በተለያየ ቅርፅ በተዘጋጀው የመኖሪያ ቤት ግንባታ መርሃ ግብር ተሳታፊ በመሆን ሕብረተሰቡ የከተማው አስተዳደር ለጀመረው የልማት እንቅስቃሴ እንደከዚህ በፊቱ ሁሉ ግንባር ቀደም ተዋናይ እንዲሆን በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

የከተማዋ አስተዳደር ህዝቡ በምርጫው ለሰጠው ቀጣይ ኃላፊነት የተሰማውን ታላቅ አክብሮት እየገለፀ የጀመራቸውን የልማትና የእድገት እንቅስቃሴዎችን በማጠናከር መዲናችን የአፍሪካና የአለም ዲኘሎማቶች ቀዳሚ ምርጫ እንደሆነች እንድትቀጥል የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል መግለፅ ይወዳል፡፡

የከተማችንም ነዋሪዎች እንደ ከዚህ በፊቱ ሁሉ ከአስተዳደሩ ጎን በመሰለፍ የመዲናዋን ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎች ከስሩ በመፍታት ከተማችን ውብ፣ ምቹና ለኑሮ ተስማሚ የማድረግ ስራችንን አጎልብተን እንድንቀጥል ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

            የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

 

 

ሳምንታዊ የአቋም መግለጫ 19/18/05

በማህበራዊ፣ኢኮኖሚያዊና መልካም አስተደደር ሥራዎች እስካሁን የተገኘውን ውጤት የበለጠ ለማጠናከር በጋራ እንስራ

 

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ2ዐዐ5 በጀት ዓመት ሕዝቡን የልማትና መልካም አስተዳደር ውጤቶች ተጠቃሚ ለማድረግ በታቀደው እቅድ መሠረት ባለፉት 9 ወራት የተሰሩ ሥራዎችን ገምግሟል፡፡

 የከተማው አስተእደር የበጀት ዓመቱ እቅድና የባለፉትን 4 ዓመታት እቅድ አፈፃፀም ትምህርት በመውሰድ፣ የህዝቡን ዋነኛ የልማትና መልካም አስተዳደር ፍላጐትና ጥያቄዎች መሠረት በማድረግና የከተማዋን የወደፊት ራዕይ ለማሳካት፣ አለም አቀፍና አህጉራዊ ሚናዋን የምትወጣበትን አቅም ለመፍጠር የሚያስችል ሆኖ የተዘጋጀ ነበር፡፡

 በዚህም መሠረት የመንገድ፣ የመኖሪያ ቤትና፣ ማህበራዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ልማት ሥራዎች ተከናውነዋል፡፡ ዋነኛ ችግር የሆነውን ሥራ አጥነትና የኑሮ ውድነት ለማቃለል በተለያዩ የጥቃቅንና አነስተኛ ዘርፎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል፡፡ አስተዳደሩ በአምስት ዓመት የስልጣን ዘመኑ ልዩ ትኩረት ሰጥቶት የነበረው የመልካም አስተደደር እና የተለያዩ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን የመፍታት እቅድ በዚህ የእቅድ ዘመንም በልዮ ትኩረት ሲሰራባቸው ቆይቷል፡፡ ህዝቡ ቀደም ሲል እንደነበረው የልማት ሥራዎች የዳር ተመልካች ሳይሆን በቀጥታ በመሳተፍ ጥቅሙንም በዚያው ልክ የሚያረጋግጥበት እቅድም ተግባራዊ ሆኗል፡፡ የእነዚህ ሁሉ የበጀት ዓመቱ ሥራዎች እቅድ አፈፃፀምም በህዝቡ በራሱም እየተገመገሙ የተከናወኑ በመሆኑ ውጤት ተገኝቶባቸዋል፡፡

 

 ባለፋት 9 ወራት ዋነኛ እቅድ በነበረው ለከተማዋ ነዋሪዎች የሥራ እድል የመፍጠርና በዚሁም የኑሮ ውድነትን የመቀነስ ተግባር ከ165 ሺህ ለሚበልጡ የከተማዋ ነዋሪዎች በተለያዩ ዘርፎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል፡፡

በጋራ መኖሪያ ቤቶች ልማት በዓመቱ ከ95 ሺህ በላይ ቤቶችን ግንባታ ለመጀመርና ከ36 ሺህ በላይ ቤቶችን ለተጠቃሚዎች ለማስተላለፍ በታቀደው መሠረት ባለፈው ዓመት የተጀመሩትን ጨምሮ የቤቶቹ ግንባታ በመፋጠን ላይ ነው፡፡ ለተጠቃሚዎች ለማስተላለፍ የተያዘው እቅድም በሁለት ዙሮች ከ2ዐ ሺህ የሚበልጡ ቤቶችን በማስተላለፍ በአጠቃላይ ከ1996 ዓ/ም ጀምሮ እስካሁን ከ11ዐ ሺህ በላይ ሰዎችን የቤት ባለቤትና በአማካኝ ከ55ዐ ሺህ በላይ ቤተሰቦችን ደግሞ የቤት ልማቱ ቀጥተኛ ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል፡፡

 

በመንገድ ልማት የቀላል ባቡር ኘሮጀክትን ጨምሮ ሰፋፊ የመንገዶች ኘሮጀክቶች በተያዘላቸው እቅድ መሠረት እንዲጠናቀቁ እየተደረገ ሲሆን የመንገዶቹን የጥራት ደረጃ ለማሳደግም እየተሰራ ነው፡፡ 

 

የጤናና የትምህርት አገልግሎቶችን ጥራት ለማሳደግ ተደራሽና ቀልጣፋ ለማድረግም በርካታ ሥራዎች ተሰርተዋል፡፡ እነዚህና ሌሎች ህዝቡን በቀጥታና በተዘዋዋሪ ተጠቃሚ የሚያደርጉና የከተማዋን እድገት የሚያፋጥኑ የልማት ሥራዎች ባለፉት 9 ወራት የተከናወኑ ሲሆን ከዚህም ጐን ለጐን ለበርካታ ጊዜያት በተገልጋዮችና ነዋሪዎች ቅሬታ ይቀርብባቸው የነበሩ ጉዳዮችን በክትትልና ቁጥጥር ስርዓትና በህዝቡም በራሱ ጥያቄ በመለየት ምላሽ እንዲሰጣቸው ተደርጓል፡፡ እስከ አሁን ድረስ ምላሽ ባላገኙ ጉዳዮች ላይ ቀጣይ ምላሽ በመስጠት የህዝብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አስተዳደሩ አቋም ይዞ እየሠራ ይገኛል፡፡

በቀጣዮቹ የበጀት ዓመቱ 3 ወራትም ቀሪውን የዘመኑን እቅድ ለማጠናቀቅ ያለአግባብ መጥቀምና መጠቀም አመለካከትና ድርጊቶችን ለመግታትና የአመራሩንና የሠራተኛውን  

አቅም በማጠናከር ህዝቡን ይበልጥ ለማገልገልና ለከተማዋ ሁለንተናዊ እድገት ይበልጥ መስራት እንደሚገባ ታምኖበታል፡፡

በየዘርፉ ያለ የአመራር፣ ያለአግባብ መጥቀምና መጠቀም፣ የህዝብ አገልጋይነት አለመኖር ችግሮችን ለመፍታት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሁሉም መዋቅሮች ያሉ አመራርና ሠራተኞች በበለጠ ቅንጅት እንዲሰሩ ይደረጋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እነዚህን ሥራዎች ይበልጥ በማጠናከር ህዝቡን ተጠቃሚ ለማድረግና የከተማዋን እድገት ለማፋጠን እንደሚሰራ እየገለፀ የከተማዋ ነዋሪዎች በተለያየ መዋቅር የሚሰሩ አመራርና ሠራተኞች ባለሃብቶችና ሁሉም አካላት ከአስተዳደሩ ጋር በጋራ እንዲሰሩ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

 

                              የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

 

 

 

 

 

 

ሳምንታዊ የአቋም መግለጫ11/08/2005

ለወረዳ ምክር ቤት አባላት ምርጫ በንቃት በመሳተፍ መብታችንንና ጥቅማችንን እናስጠብቅ

 

የዜጐች ማህበራዊ፣ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ተሳትፎና ጥቅም በላቀሁኔታ ሊረጋገጥ የሚችለው ራሳቸው ዜጐች በቅርብ የሚመራቸውን አካላት ለመምረጥ በቀጥታና በተወካዮቻቸው አማካኝነት በሚያደርጉት ተሳትፎ ነው፡፡ ይህ ካልሆነ ግን በአንድ አጋጣሚ መሪዎቻቸው የመሆን እድሉን ባገኙ አካላት ፍላጐትና ውሳኔ ብቻ ለመተዳደር መገደዳቸው አይቀሬ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የመላውን ህዝብ ፍላጐትና ጥቅም በህዝብ ቀጥተኛ የላቀ ተሳትፎ ማረጋገጥ አያስችልም፡፡

 የሰው ልጅን ፍላጐትና ጥያቄ በራሱ እንዲመራ ለማድረግ ለነፃነት፣ ለሠላምና ለደህነነቱ የሚበጀውን ስልት በመቀየስ በተለይም ከ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ በአሜሪካና አውሮፖ ሃገራት የምርጫ ስርዓትን ተግባራዊ ሲደረግ ቆይቷል፡፡ በዚህም ዜጐች ይበልጥ ይጠቅመናል፣ይመራናል፣ ለማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞች፣ ባህላዊ እሴቶች ይወክለናል የሚሉትን በመምረጥ ሲተዳደሩ ቆይተዋል፡፡

 በሃገራችንም መሰረቱ ከተጣለበት የዘውዳዊው የአጼ ኃ/ሥላሴ ሥርዓት ከ1923 ዓ/ም የተጀመረ ቢሆንም በዚያ ዘመንና በወታደራዊ ደርግ ዘመን ይካሄድ የነበረው ምርጫ በህዝቡ ተሳትፎ ሳይሆን በራሳቸው በመኳንንቱና በባለሥልጣናቱ እንዲሁም ከእነሱ ጋር በጥቅም በተሳሰሩ ቤተሰቦች፣ወዳጆቻቸው እና የጥቅም ተካፋዮች ይካሄድ ነበር፡፡ ዴሞክራሲያዊና መላውን ሕዝብ በቀጥታና የተለያየ አመለካከትና ኘሮግራም ያላቸውን የፓለቲካ ፖርቲዎችን ያሳተፈ ምርጫ ማካሄድ የተጀመረው ግን ሃገራችን በፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፓብሊክ መንግስት መመራት ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ ነው፡፡

አሁን የሃገራችን ህዝቦች የተፈጠረላቸውን ምቹ ሠላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሁኔታ በመጠቀምና በምርጫ በመሳተፍ የሚያገኙትን ጥቅም በመረዳት በአጠቃላይ የምርጫ ሂደትና ድምፅ በመስጠት ባለፉት 4 ሃገር አቀፍ ምርጫዎች በአካባቢ ም/ቤት አባላትና ማሟያ ምርጫዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡ በምርጫዎቹ ባረጋገጡት የባለቤትነት ተሳትፎም ጥቅሞቻቸውን አረጋግጠዋል፡፡ እያረጋገጡም ይገኛሉ፡፡

 የዚህ አካል የሆነው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና የክ/ከተማ ምክር ቤቶች አባላት ምርጫ ሚያዚያ 6 ቀን 2ዐዐ5 ዓ/ም የተካሄደ ሲሆን በነገው እለት ሚያዚያ 13 ቀን 2ዐዐ5 ዓ/ም የወረዳ ምክር ቤቶች አባላት ምርጫ ይካሄዳል፡፡

 በምርጫው የመጨረሻው ለህዝብ በቅርበት የሚሰሩ የምክር ቤት አባላት የሚመረጡ ሲሆን የሕዝብ ተመራጮቹ በቅርበት የህዝቡን ችግርና ቅሬታ በማዳመጥ ለእያንዳንዱ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የሚሰሩ በመሆኑ የከተማችን ነዋሪዎች ትኩረት ሰጥተው በምርጫው ድምፅ በመስጠት መሳተፋቸው ጠቀሜታው የላቀ ነው፡፡ ሂደቱም ነፃ፣ ሠላማዊ፣ ፍትሐዊ ዴሞክራሲያዊና ተአማኒነት ያለው ሆኖ እንዲጠናቀቅ የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡

 ባለፈው እሁድ ሕዝቡ የከተማና ክ/ከተማ ምክር ቤቶች አባላት ምርጫ በሠላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ሰፊ ተሳትፎ በማድረጉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አድናቆቱና አክብሮቱ የላቀ ነው፡፡ አሁንም መላው የከተማችን ነዋሪዎች ነገ እሁድ ሚያዚያ 13 ቀን 2ዐዐ5 ዓ/ም በሚካሄደው የወረዳ ም/ቤት አባላት ምርጫ በመሳተፍ ባለፈው እሁድ ያሳዩትን የባለቤትነትና የትብብር መንፈስ እንዲደግሙት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከወዲሁ ያሳስባል፡፡ እምነቱና ተስፋውም የላቀ ነው፡፡

 በዚህ የወረዳ ምክር ቤት አባላት ምርጫ በ116 ወረዳዎች በሚገኙ 1 ሺህ 523 የምርጫ ጣቢያዎች ከ1 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ለመራጭነት የተመዘገቡ የከተማችን ነዋሪዎች ድምፅ እንደሚሰጡ ይጠበቃል፡፡ ከ34ሺህ በላይ ተወዳዳሪዎችም በሕዝብ ፊት ለመወዳደር ቀርበዋል፡፡

 በዚሁ አጋጣሚ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እንዳለፈው ሳምንት የከተማና ክ/ከተማ ምክር ቤቶች አባላት ምርጫ ሁሉ ነፃ፣ሠላማዊ፣ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊና በሕዝብ ተአማኒነት ያለው ሆኖ እንዲጠናቀቅ ከመንግስት የሚጠበቀውን ሁሉ እንደሚያደርግ ይገልፃል፡፡ የመራጭነት ካርድ የወሰዱ ነዋሪዎችም በመምረጥ፣ተወዳዳሪ የፖለቲካ ፖርቲዎችና ተወካዮቻቸው ሕግና መመሪያውን ተከትለው እንዲሰሩ በመተባበር፣የምርጫ አስፈፃሚዎችም በአግባቡ እንዲያስፈጽሙና የሕዝቡን ፍላጐት እንዲያሳኩ፣ በጋራ በመቆም ፍላጐታቸውንና ጥቅሞቻቸውን ያስከብሩ ዘንድ መልዕክቱን ያስተላልፋል፡፡ ሰፊና በኃላፊነትና በባለቤትነት የተሞላ የሕዝብ ተሳትፎ ለማረጋገጥ ምርጫውን ያለምንም እንከን ለማሳካት ሁላችንም በጋራ እንስራ፡፡

                                             የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

 

 

 

ሳምንታዊ የአቋም መግለጫ08/08/2005

የመምረጥ ዴሞክራሲያዊ መብታችንን በሚገባ በመጠቀም የህዝብ ውሳኔ ሰጪነታችንን እናረጋግጥ፡፡

 

ዜጐች በሃገራቸው ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሁለንተናዊ ሥራዎች ላይ ተሳትፎ ማድረጋቸው ያለው ጥቅም ለራሳቸው ለዜጐችና ለሃገራቸውም ወሳኝነት ያለው ነው፡፡ ይህ ሳይሆን ቢቀር ግን ፍላጐቶቻቸውም ሆነ የሃገር እድገት በአንድ የተለየ አጋጣሚ መሪዎቻቸው የመሆን እድሉን ባገኙ አካላት ፍላጐትና ውሳኔ ብቻ እንዲሆን የግድ ይሆናል፡፡

ከ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ በአሜሪካና አውሮፖ ሃገራት ማበብ የጀመረው ህዝቦች ተወካዮቻቸውን የመምረጥ ወይም ምርጫ ሂደትም ዜጐች ይበጀናል ያገለግለናል የሚሉትን መሪ በቀጥታ የሚመርጡበት፣ የመረጡትም መሪ ወይም ተወካያቸው ለመረጡት አካላት ደህንነት፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም ሰብዓዊ ፍላጐት የሚሰራበት፣ ይህን ማድረግ ካልቻለ ግን እንደገና በህዝብ ውሳኔ የተሰጠውን ውክልና የሚነጠቅበት ሂደት በመሆኑ ዜጐች በራሳቸውና በሃገር ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ውስጥ የሚሳተፉበት ተግባር ነው፡፡

በሃገራችንም ምንም እንኳን ለታሪኩ መጀመር መሰረት የተጣለበት ከዘውዳዊው የአጼ ኃ/ስላሴ ሥርዓት ከ1923 ዓ/ም ጀምሮ ቢሆንም ለመሰረታዊ የምርጫ መርሆች በተለይም ለህዝብ ውሳኔ ሰጪነት ግን ቦታ አልነበረውም፡፡ "ህዝቡ መምረጥ እስከሚችል" በሚል የምክር ቤት አባላት ይመረጡ የነበረው በራሳቸው በንጉሱና በመኳንንቱ ለመሆኑ በአዋጅ ጭምር የተደነገገ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ባለው የደርግ ዘመን መንግስትም ቢሆን የነበረው ምርጫ ምልአተ ህዝቡን ያሳተፈና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓቱን የጠበቀ አልነበረም፡፡

በሽግግር ዘመንና ሃገራችን በፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፖብሊክ መንግስት መመራት ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ ግን የሃገራችን ህዝቦች ለዘመናት ይሹት የነበረውና የብዙዎች ትግል ፍሬ የሆነው የዴሞክራሲያዊ ምርጫ ሂደት በህገ መንግስቱ ተደንግጐና ነፃ፣ገለልተኛና ፍትሃዊ ምርጫ የሚያካሂድ ሲቪል ተቋም የኢትዮጵያ ብሂራዊ ምርጫ ቦርድ ተቋቁሞ 4 ሃገር አቀፍ ምርጫዎችና በርካታ የአካባቢ ማሟያና የህዝበ ውሳኔ ምርጫዎች ተካሂደዋል፡፡

በዚህም የሃገራችን ህዝቦች መሪዎቻቸውን የሚመርጡበትን ፖለቲካዊና ውሳኔ ሰጪነት ተግባር እያዳበሩ ከመምጣታቸውም ባሻገር ለሠላማዊ የሥልጣን ሽግግርና ከዚያም በኋላ በስልጣን ላይ የሚኖሩ አካላት ለህዝብ ተጠያቂና አገልጋይ መሆናቸውን በማመን እንዲሰሩ ኃላፊነት ሰጥቷል፡፡

በተለይም ነዋሪዎች በቅርበት የሚያውቋቸውንና የልማት፣ የመልካም አስተዳደርና የዴሞክራሲ፣ የዕለት ተዕለት ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጥቅማቸውን ያስጠብቁልኛል ብለው የሚያመኗቸውን ተወካዮቻቸውን የሚመርጡበት የአካባቢ ምክር ቤት አባላት ምርጫም በሠላማዊ፣ዴሞክራሲያዊና ተዓማኒነት ያለው ሆኖ መከናወን ይኖበታል፡፡

በከተማችን አዲስ አበባም ይህ የምርጫ ሂደት በነገው እለት ሚያዚያ 6 እና በቀጣዩ ሳምንት ሚየዚያ 13 የሚካሄድ ይሆናል፡፡ በዚህም መሠረት ነገ ሚያዚያ 6 ቀን 2ዐዐ5 ዓ/ም የከተማ አስተዳሩ ምክር ቤት አባላት እና የክፍለ ከተማ ም/ቤት አባላት ምርጫ ይካሄዳል፡፡ በቀጣዩ ሳምንት ሚያዚያ 13 ቀን 2ዐዐ5 ዓ/ም ለህብረተሰቡ ይበልጥ በቅርበት የሚሰሩ የወረዳ ምክር ቤት አባላት ምርጫ ይካሄዳል፡፡ 

የአካባቢ ምክር ቤት አባላት ምርጫ ሂደት ተወዳዳሪ የፖለቲካ ፖርቲዎች ምልክቶቻቸውን እንዲወስዱ ከተደረገበት ህዳር ወር ጀምሮም በወጣው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ሁሉም ዝግጅቶች በተሳካ ሁኔታ ተካሂደዋል፡፡

11 የፖለቲካ ፖርቲዎችም ለከተማ አስተዳደሩ ምክር ቤት 138፣ በየወረዳዎች ለ3ዐዐና በክ/ከተሞች ደግሞ ከ3ዐዐ እስከ 4ዐዐ ለሚደርሱ መቀመጫዎች ለመወከል ተወዳዳሪዎቻቸውን አቅርበው የምርጫ ህጉ በሚፈቅደው መሠረት ቅስቀሳና መሰል ዝግጅቶችን አድርገዋል፡፡

በከተማዋ 116 ወረዳዎች በሚገኙ 1ሺህ 523 የምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ አስፈፃሚዎች በቂ ግንዛቤ አግኘተው የቁሳቁሶች ዝግጀትም ተጠናቋል፡፡ በከተማችን በመራጭነት ካርድ የወሰዱ ከ1 ሚሊየን የሚበለጡ መራጮችም በነገው እለትና በቀጣዩ ሳምንት በሚካሄዱት ምርጫዎች ካርዳቸውን ይበጀናል ለሚሉት ፖርቲና ተወካይ ድምፅ እንደሚሰጡ ይጠበቃል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የምርጫው ሂደት እስካሁን በነበረው ሠላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ከመንግስት የሚጠበቀውን ሁሉ እንደሚያደርግ በዚህ አጋጣሚ እየገለፀ የመራጭነት ካርድ የወሰዱ ነዋሪዎች በመምረጥ፣ ተወዳዳሪ የፖለቲካ ፖርቲዎችና ተወካዩቻቸው ህጉንና መመሪያዎችን ተከትለው በመስራት፣ የምርጫ አስፈፃሚ አካላትም የተጣለባቸውን ኃላፊነት በሚገባ በመወጣትና መላው የከተማችን ነዋሪዎችና የሚመለከታቸው ሁሉ ምርጫው ሠላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊ፣ ፍትሃዊና በመላው ህዝብና ፓርቲዎችም ተዓማኒነት ያለው ሆኖ እንዲጠናቀቅ የየድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

                                         የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

 

 

 
More Articles...
English (United Kingdom)
Addis looks like
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa
  • Addis Ababa